bt Abraham Tube ቤተ አብርሃም Premiere

❇️✞❇️ ታኅሣሥ 12  ❇️✞❇️

❇️✞❇️ እንኩዋን ለታላቁ ጻድቅ "አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ" እና ለሰማዕታት "አንቂጦስ ወፎጢኖስ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ❇️✞❇️

+*" አባ ሳሙኤል ዘዋሊ "*+

=>ሃገራችን እልፍ አእላፍ ቅዱሳንን አፍርታለች:: እንኩዋን በተባረከው በቀደመው ዘመን ይቅርና ዛሬም ከሃገር ተርፈው ለዓለም የሚጸልዩ : በየበርሃውና በየፈርኩታው የወደቁ ብዙ አባቶችና እናቶች አሉን::

+በኢትዮዽያ ውስጥ ከተነሱ ቅዱሳን "ሳሙኤሎች" ልዩ ቦታ አላቸው:: በ20 ዓመታት ልዩነት ብቻ 6ቱ ሳሙኤሎች ተነስተው ከቅድስና ሕይወት እስከ ስብከተ ወንጌል : ከገዳማዊ ሕይወት እስከ ምናኔ በጐውን ጐዳና አሳይተዋል::

+እነዚህም:-
1.ሳሙኤል ዘዋልድባ
2.ሳሙኤል ዘጣሬጣ
3.ሳሙኤል ዘቆየጻ
4.ሳሙኤል ዘግሺ
5.ሳሙኤል ዘሃሌ ሉያ እና
6.ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ናቸው::

+በተመሳሳይም በግብጽ የደብረ ቀልሞኑን ኮከብ ጨምሮ (መልአኩን ቀውስጦስን ከጌታ ያማለዱት) ብዙ ሳሙኤሎች ተነስተዋል:: የድሮ እናቶቻችን በእውነት ስም መሰየሙን ይችሉበታል:: "ሳሙኤል" ማለት "ሰምዓኒ እግዚአብሔር ስዕለትየ - እግዚአብሔር ልመናየን ሰማኝ" ማለት ነውና::

+ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ታላቁ ኢትዮዽያዊ ጻድቅ አቡነ ሳሙኤል ዘዋሊ የተወለዱት በ13ኛው መቶ ክ/ዘመን (በ1295) በምድረ አክሱም ነው:: ወላጆቻቸውም እስጢፋኖስና ዓመተ ማርያም ይባላሉ::

+የዘር ሐረጋቸው ከካህናት ወገን ነውና ጻድቁ ገና በልጅነት ምሥጢራተ ሃይማኖትን ጠጥተዋል:: ለዚህም ይመስላል ገና ሕጻን ሳሉ ምናኔን የተመኙት::

+ከልጅነታቸው ጀምረው ወላጆቻቸውን ያገለገሉት ሳሙኤል ትምሕርታቸውን ሲፈጽሙ የተጉዋዙት ወደ ደብረ በንኮል ነበር::
በጊዜውም የጻድቁ ወላጆች ዐርፈው እንደ ነበር ይነገራል:: ደብረ በንኮል ማለት የታላቁ ኮከብና አበ መነኮሳት አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ገዳም ነው::

+መድኃኒነ እግዚእ ለሃገር ብርሃን የሆኑ ቅዱሳንን ያፈሩ ዘንድ ሲተጉ እግዚአብሔር 7ቱን ከዋክብት ሰጣቸው:: ክእነዚህ መካከልም ቀዳሚው አቡነ ሳሙኤል ናቸው:: ቀሪዎቹ ደግሞ እነ አቡነ ያሳይ ዘመንዳባ : ሳሙኤል ዘጣሬጣ : ሳሙኤል ዘቆየጻና ያፍቅረነ እግዚእ ዘጉጉቤን የመሰሉ ናቸው::

+አቡነ ሳሙኤል ከ6ቱ ባልንጀሮቻቸው ጋር ሆነው በደብረ በንኮል ተጋድሎን አሐዱ አሉ:: እንጨት ይሰብራሉ:: ውሃ ይቀዳሉ:: እህል ይፈጫሉ:: በፍጹም ልባቸውም ይታዘዛሉ:: ጐን ለጐን ደግሞ ከቅዱሱ አበ ምኔት መድኃኒነ እግዚእ ጽንዓትን : ትሕትናን : ትሕርምትን ይማሩ : ሥርዓተ ገዳምንም ያጠኑ ነበር::

+ከአገልግሎታቸው ማማር የተነሳ ሁሉን ደስ ማሰኘት ቻሉ:: በዚህ ጊዜም ጻድቁ አበ ምኔት አቡነ ሳሙኤል ዘዋሊንና 6ቱን አበው ጠርተው ለምንኩስና አቀረቧቸው:: "ይገባቹሃል!" ሲሉም ከአሞክሮ ወደ ምንኩስና አሸጋገሯቸው::

+በዚያች ቀን 7ቱ ሲመነኩሱ ከሰማይ ብርሃን ወርዶ በመታየቱ ቅዱሳኑ "ከዋክብት ብሩሃን" ተባሉ:: ለተወሰነ ጊዜም በዚያው በገዳሙ አገለገሉ:: የአቡነ ሳሙኤል ዘመዶች ግን እየመጡ ጻድቁን ስላስቸገሩ 7ቱም ቅዱሳን ተመካክረው : ከአባታቸው መድኃኒነ እግዚእ ተባርከው ከደብረ በንኮል ወጡ::

+ሁሉም መንፈስ ቅዱስ ወደ መራቸው ሲሔዱ 3ቱ (ማለትም ሳሙኤል ዘዋሊ : ያሳይ ዘመንዳባና ያፍቅረነ እግዚእ ዘጉጉቤ) ወደ ጣና ሔዱ:: በዚያም ለጥቂት ጊዜ አብረው ከቆዩ በሁዋላ ለአገልግሎት ተለያዩ:: አቡነ ያሳይ "መንዳባን" : አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ "ጉጉቤን" ይዘው እዛው ጣና አካባቢ ሲቀሩ አባ ሳሙኤል ወደ ዋልድባ ሔዱ::

+ዋልድባ በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን በጌታ ፈቃድ የተመሠረተ ሲሆን 860ው መሥራች ቅዱሳን በመሠወራቸው እንደ ጠፍ ይቆጠር ነበርና አቡነ ሳሙኤል እንደ ገና አቀኑት::

+ጻድቁ በዋልድባ የመጨረሻውን ትሕርምት ከመያዛቸው በፊት በጊዜው ከፍተኛ የሆነ የወንጌል አገልግሎት ሰጥተዋል:: ቀጥለውም ኑሯቸውን ከግሩማን አራዊት ጋር አድርገዋል:: በስዕለ አድኅኖው እንደምናየው ለዘመናት በአንበሳ ጀርባ ላይ ተጭነዋል::

+ጧት ማታም ብዙ ግሩማን አራዊትን እያስከተሉ ለአገልግሎት ደክመዋል:: ጻድቁ ከትሕርምት ብዛት እህል ትተው የሻገተ ጐመንና መልኩን የለወጠ ውሃን ለቁመተ ሥጋ ይጠቀሙ ነበር::

+አንድ ቀንም መድኃኒታችን ክርስቶስ ወደ እርሳቸው መጥቶ ባረካቸው:: አካላቸውንም በቅዱስ ምራቁ አትቦ ቀባቸው:: በዚህ ጊዜም ኃይለ መንፈስ ቅዱስን ተመሉ:: የክርስቶስን ሕማማት እያሰቡም እልፍ ጊዜ ይሰግዱ: ጀርባቸውን ይገርፉም ነበር::

+እግራቸውን በሰንሰለት አሥረው ይጋደሉም ነበር:: በዚህ ግብራቸው አጋንንትን አሳፍረው: ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኙ:: ከቆይታ በሁዋላም ዋልድባ በመነኮሳት ተሞላ:: ደቀ መዛሙርት በዙ:: ቀዳሚው ግን አባ ዘሩፋኤል ጻድቅ ነው::

+አቡነ ሳሙኤል ከድንግል እመቤታችን ጋር ልዩ ፍቅር ነበራቸው:: ዘወትር ውዳሴዋንና ቅዳሴዋን በተመስጦ ያደርሱላት: ፈጽመውም ያመሰግኗት ነበር:: ይህንን ሲያደርጉ ከመሬት ክንድ ከፍ ብለው ይንሳፈፉ ነበር::

+ተከታዮቻቸው ሲርባቸውም ውሃውን በቅዳሴ ማርያም ነጭ ሕብስት ያደርጉት ነበር::

"ሶበ አተቦ ለማይ በቅዳሴኪ እንዘ ይጼሊ::
ረሰዮ ሕብስተ ሳሙኤል ጽጌ ሃይማኖት ዘሐቅለ ዋሊ::
ምሕረተ ወፍትሐ ለተአምርኪ እኅሊ::
ስረዪ ኃጢአትየ ወዕጸብየ አቅልሊ::
እስመ ኩሎ ገቢረ ማርያም ትክሊ::" እንዳለ ሊቁ:: (ማኅሌተ ጽጌ)

+እመ ብርሃንም ስለ ፍቅር ነጭ እንቁ ሰጠቻቸው:: ሰማያዊ ሕብስትን መገበቻቸው:: ንጹሕ ዕጣንንም አበረከተችላቸው:: ለ12 ዓመታትም ከሰማይ ካህናት ጋር አጠኑ:: ድንግል ማርያም "እንዳንተ ውዳሴየንና ቅዳሴየን በፍቅር የሚደግምልኝን አማልደዋለሁ" ስትላቸው:-

+ጌታ ደግሞ ገዳማቸውን ዋልድባን ቀድሷታል:: ቀድሞም በስደቱ ባርኩዋት ነበር:: የጻድቁ ዜና ፈጽሞ ብዙ ነውና ለዛሬ በዚህ ይብቃን:: የዋልድባው ኮከብ አቡነ ሳሙኤል ያረፉት ታሕሳስ 12 ቀን በ1395 ሲሆን ዕድሜአቸውም 100 ዓመት ነበር::

<< ለጻድቁ ክብር ይገባል !! >>

+"+ ቅዱሳን አንቂጦስ ወፎጢኖስ +"+

=>እነዚህ ቅዱሳን በሥጋ ወንድማማቾች ሲሆኑ የዘመነ ሰማዕታት ፍሬዎች ናቸው:: ዜና ሕይወታቸውን ሳስበው ይገርመኛል:: በእሳት የወጣትነት ዘመናቸው በሃይማኖት ጸንተው: ፍቅረ ክርስቶስ እንደ እሳት በላያቸው ላይ ይነድ ነበር::

+በእውነት ክርስቶስን በከንፈር ያይደለ በፍጹም ልቡና መውደድ እንዴት ያለ መታደል ነው! ክርስቶስን የወደደ የድንግል እናቱና የቅዱሳን ወዳጆቹ ፍቅር ይበዛለታል እንጂ አይቀንስበትም::

+ቅዱሳኑ አንቂጦስና ፎጢኖስ ወጣትነት: የዓለም ኑሮ ሳያታልላቸው ለሰማዕትነት ራሳቸውን አዘጋጁ:: እንኩዋን ሰውን አራዊትን የሚያስበረግግ የስቃይ ዓይነት ተሰልፎ ሳለ በፍጹም አልደነገጡም::

+መጀመሪያ አንቂጦስን አቀረቡት:: ገረፉት: ምንም አልሆነም:: በእሳት አቃጠሉት: ምንም አልነካውም:: ለአንበሳ ሰጡት: እነርሱ ግን ሰገዱለት:: ከዳር ሆኖ ይህንን ሁሉ ሲመለከት የነበረው ወንድሙ ፎጢኖስ ዘሎ ወደ መከራ አደባባይ ገባ::

+"ወንድሜ የክርስቶስ ነውና መቼም አታሸንፈውም" ሲል ጮኸ:: በዚህ ጊዜም በሥፍራው የነበሩ ብዙ አሕዛብ "የእነዚህ ወጣቶች አምላክ አምላካችን ነው" አሉ::
መኮንኑም 2ቱን ቅዱሳን ከብዙ ሕዝብ ጋር አሰይፏቸዋል::

+እንደ እኔ ያለ ኃጢአተኛም በስማቸው እንዲህ ሊጸልይ ይገባል:-"ሰላም ዕብል ለአንቂጦስ ማሕበሮ::
እለ በእሳት ፈጸሙ ረዊጸ ወተባድሮ::
ያብጽሑኒእሉ ምስለ መላእክት ድርገተ ዘምሮ::
ህየ አኀሉ ወሬዛ ነዳየ ኩሉ አዕምሮ::
ኀበ ይዘብጣ ደናግል ከበሮ::" (አርኬ)

=>አምላከ ሳሙኤል በምጃቸው ሃገራችን ከጦርነት: ሕዝቦቿን ከስደት ይሰውርልን:: ሞልቶ ከተረፈ በረከታቸውም አይንሳን::

=> ታሕሳስ 12 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ
2.ቅዱሳን አንቂጦስ ወፎጢኖስ (ሰማዕታት)
3.አባ ነድራ
4.ቅዱስ ዮሐንስ ተአማኒ
5.ጉቡዓን ኤዺስ ቆዾሳት

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ላሊበላ ጻድቅ (ንጉሠ ኢትዮዽያ)
3.ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ
4.ቅዱስ ቴዎድሮስ ምሥራቃዊ (ሰማዕት)
5.ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ
6.ቅዱስ ማቴዎስ ሐዋርያ
7.ቅዱስ ድሜጥሮስ ሊቅ

❇️ የሚያሳድዷችሁን መርቁ . . . ደስ ከሚላቸው ጋር ደስ ይበላችሁ:: ከሚያለቅሱም ጋር አልቅሱ:: እርስ በርሳችሁ በአንድ አሳብ ተስማሙ:: የትዕቢትን ነገር አታስቡ:: ነገር ግን የትሕትናን ነገር ለመሥራት ትጉ:: +"+ (ሮሜ. 12:14-16)

    <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>

1 day ago | [YT] | 3